ቀጣዩን እዚህ ገጽ ላይ ያንብቡ
ከ536 መቀመጫዎች የአቶ መለስ ቡድን 534 ቱን አሸነፈ ተባለ
ምርጫ ቦርድ ባወጣዉ ዘገባ፣ አራቱ በኢሕአዴግ ዉስጥ ያሉ ግንባሮች እንዲሁም በአፋር በሶማሌ በጋምቤላ በሃረሬ ..ያሉ የገዢዉ ፓርቲ ተቀጥያዎች፣ ይፋ ከተደረጉት ከ 536 መቀመጫዎች 534 ቱን ማሸነፋቸዉን ምርጫ ቦርድ አሳወቀ።
ከ536 ቱ ዶር አሸብር የሚባሉ አንድ የግል ተወዳዳሪ በደቡብ ክልል፣ አንድ የመድረኩ ተወዳዳሪ ደግሞ በአዲስ አበባ አሸናፊ ተብለዋል።
የስነ ምግባር ደንቡን የፈረሙና በወቅቱ ለገዢዉ ፓርቲ መጠነኛ አለም አቀፍ ድጋፍ ያስገኙለት መኢአድ፣ ኢዴፓና የአየለ ጫሚሶ ቡድን፣ ኢሕአዴግ ከዘረፈዉ ትንሽ ያቀምሳቸዋል ተብሎ ቢጠበቅም፣ በዜሮ ተመልሰዋል።
በሶማሌ ክልል 2፣ በጋምቤላ 1፣ በቤኔሻንጉል 7 ፣ በአማራዉ ክልል 1 ፣ በአጠቃላይ በ 11 መቀመጫዎች ገና ይፋ ያልተደረጉ ቢሆኑም፣ እነዚህም ገዢዉ ፓርቲ እንደሚወስዳቸዉ ብዙዎች ይገምታሉ።
በዚህ ምክንያት በሚቀጥለዉ ፓርላማ ተቃዋሚዎች 2 ብቻ በመሆናቸዉ አስተያየት ለመስጠት ሰፊ ጊዜ ይኖራቸዋል ተብሎ ይጠበቃል።
ግንቦት 16 ቀን 2002 ዓ.ም – 5፡40 AM DC Time
በርካታ የመድረክ መሪዎች «ተሸናፊ» ናቸዉ እየተባሉ ነዉ
ከአዲስ አበባ የደረሱን አንዳንድ መረጃዎች እንደሚገልጹት የመድረክ፣ የመኢአድና የኤዴፓ በርካታ አመራር አባላት ተቸነፉ እየተባለ ነዉ። በአዲስ አበባ ኢንጂነር ግዛቸዉ፣ ዶር ኃይሉ አርዓያ፣ አቶ ሃይሉ ሻዉል፣ ዶር ነጋሶ ጊዳዳ፣ አቶ ተመስገን ዘዉዴ፣ አቶ አንዱዋለም አርጌ፣ አቶ አሥራት ጣሴ እንዲሁም ሌሎች ተሸነፊ ናችሁ ሲባል በአምቦ ዶር መራራ ጉዲና በሃዲያ ፕሮፌሰር በየነ ተመሳሳይ እድል ገጥሟቸዋል።
የመድረክ አመራር አባላት ምርጫዉን በተመለከተ ተመሳሳይ አስተያየት ትላንት መስጠታቸዉ ይታወቃል። ኢንጂነር ኃይሉ ምርጫዉ ጨዋታ እንደሆነ የገልጹ ሲሆን ዶር መራራ ጉዲና በአፍሪካ ከተደረጉ ምርጫዎች ጋር እንኳን ቢነጻጸር ተደረገ የተባለዉ ምርጫ፣ ምርጫ እንዳልሆነ ተናግረዋል። ኢንጂነር ግዛቸዉም ምርጫዉ ነጻና ዴሞክራሲያዉ አይደለም ብለዉታል።
በመኢአድ/ኤዴፓ/ሕወሃት-ኢሕአዴግና የአየለ ጫሚሶ ቡድን ተዘጋጅቶ እንደ ትልቅ ነገር ሲቆጠር የነበረዉ፣ በሼራተን የተፈረመዉን ሕግ የሆነዉ የሥነ-ምግባር ደንብ ጥሰሃል በሚል ሕወሃት/ኢሕአዴግ በኢንጂነር ግዛቸዉ ላይ ከፍተኛ ጥቃት ሲሰነዝር ማምሸቱ ይታወቃል። ኢንጂነር ግዛቸዉ በርግጥ ከዚህ ሕግ ደንብ ዉጭ ምርጫዉ እየተደረገ እያለ የሰጡትን አስተያየት መስጠት እንዳልነበረባቸዉ በማመን ይቅርታ ቢጠይቁም፣ ምርጫዉ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ አለመሆኑም በድጋሚ አጠንክረዉ ገልጸዋል።
ግንቦት 16 ቀን 2002 ዓ.ም – 5፡10 AM DC Time
በአዲስ አበበ ሕወሃት/ኢሕአዴግ አሸነፈ እየተባለ ነዉ
በአዲስ አበባ ምርጫ ጣቢያዎች በር ላይ የተለጠፉ ዉጤቶች እንደሚያሳዩት ሕወሃት/ኢሕአዴግ ከምርጫ ዘጠና ሰባት በፊት ተደረጉ እንደተባሉ የ1992 እና የ1987 ምርጫ በአዲስ አበባ እንዳሸነፈ እየገለጹ ነዉ።
ለምሳሌ ዶር ነጋሶ ጉዲና በተወዳደሩበት በወረዳ 18 ባሉ አራት ጣቢያዎች የሚከተሉት ዉጤቶች ተለጥፈዋል፡
1ኛ ጣቢያ ፡
ሕወሃት/ኢሕአዴግ – 205 ፤ መድረክ – 202፣ ኤዴፓ – 28 እና መኢአድ – 7 – ሌሎች ስልሳዎቹ – 0
2ኛ ጣቢያ፡
ሕወሃት/ኢሕአዴግ – 241 ፤ መድረክ – 200፣ ኤዴፓ – 21 እና መኢአድ – 23 – ሌሎች ስልሳዎቹ – 0
3ኛ ጣቢያ፡
ሕወሃት/ኢሕአዴግ – 238 ፤ መድረክ – 189፣ ኤዴፓ – 23 እና መኢአድ – 2 – ሌሎች ስልሳዎቹ – 0
3ኛ ጣቢያ፡
ሕወሃት/ኢሕአዴግ – 227 ፤ መድረክ – 166፣ ኤዴፓ – 22 እና መኢአድ – 10 – ሌሎች ስልሳዎቹ – 0
4ኛ ጣቢያ፡
በወረዳዉ ተሰጠ ከተባለዉ 1787 ድምጽ ኢሕአዴግ 911 (51%) አገኘ ሲባል ለመድረኩ 757(43%) ተሰጥቶታል። የኤዴፓዉ ዋና ጸሃፊ አቶ ሙሼ ሰሙ 94 (5%) ሲያገኙ ለመኢአድ 25 (1%) ብቻ ተሰጥቶታል።
በሌሎችም የአዲስ አበባ ወረዳዎች ተመሳሳይ ሁኔታ እንዳለ የገለጹልን ዘጋቢዎቻችን በወረዳ 18 የተለጠፈዉን የተመለከቱ ኢትዮጵያዉያን በመገረም ይስቁ እንደነበረም ገልጸዉልናል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 3፡35 PM ዋሺንግተን ሰዓት – 9፡35 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
ገዢዉ ፓርቲ በመድረክ አመራር ላይ ዘመቻ ጀመረ- የአዉሮፓ ሕብረት ታዛቢዎች ሃላፊ ምርጫዉ ጸጥታና መረጋጋት የታየበት ነዉ አሉ።
የሕወሃት/ኢሕአዴግ ቴለቭዥን የአዉሮፓ ሕብረት የታዛቢዎች ቡድን ሃላፊ የሆኑት ሚስተር ቲስ በርማን፣ በምርጫዉ ላይ የሰጡትን አጭር አስተያየት እየደጋገሙ በማቅረብ ላይ ናቸዉ። ሚስተር በርማን »ምርጫዉ ጸጥታና መረጋጋት እንደነበረ» ያሉ ሲሆን ምርጫዉ ፍትሃዎና ዴሞራሲያዊ ነዉ የሚል ቃል አልወጣቸዉም።
ጸጥታ ሰፈነ ማለት ምርጫዉ አልተሰረቀም ማለት እንዳለሆነ የሚታወቅ ሲሆን ኢቲቭ ሕዝብን ለማወናበድና በመድረኩ አመራር አባላት ላይ ጥቃት ለማድረስ የሚስተር በርማንን እየተጠቀሙበት ነዉ።
በኢንጂነር ግዛችዉ ላይ ሲደረግ የነበረዉ ጥቃት እንደተጠበቀ ሆኖ በፕሮፌሰር በየነ፣ አቶ ቡልቻ ደምቅሳና ዶር መራራ ጉዲና ላይ ኢቲቪ ተከታታይ ዉንጀላዎች ሲያቀርብ አምሽቷል።
በሌላ በኩሉ ዋላታ ኢንፎርሜሽን ማእክል አቶ በርማ የተናገሩትን በመለጠጥ «ምርጫዉ ነጻ፣ ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያአዊና ችግር የሌለበት » እንዳሉም ዘግቧል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 2፡45 PM ዋሺንግተን ሰዓት – 8፡45 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
የሕወሃት/ኢሕአዴግ ቴሌቭዥን በኢንጂነር ግዛቸዉ ላይ የከፈተዉ ጥቅት
የሕወሃት/ኢሕአዴግ ቴሌቭዥን በኢንጂነር ግዛቸዉ ላይ የከፈተዉን ጥቅት ለማዳመጥ ወደ ሚቀጥለዉ ድህረ ገጽ ይመልክቱ። ኢንጂነር ግዛቸዉ ምርጫዉ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ አለመሆኑ መረጋገጡን የገለጹበትን ቃለ ምልልስ ቆርጠዉ ጥቂት ቃላት ብቻ ነዉ ለተመልካቾች አቅርበዋል።
በዚሁ በሕወሃት/ኢሕአዴግ ቴሌቭዥን አቶ መለስ በአድዋ ድምጻቸዉን ሲሰጡ ተመልክተናል። በርካታ እናቶች አበባ ይዘዉ ትልቅ አቀባበል ሲደረግላቸዉ ነዉ ያየነዉ። ይሄም መንግስቱ ኃይለማሪያም ብቻዉን ተወዳድሮ አሸነፍኩ ያለበትንና ሰዎች አቀበባል ሲያደርጉለት የነበረበትን ምርጫ አስታዉሶናል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 2፡00 PM ዋሺንግተን ሰዓት – 8፡00 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
የኃይልና የጉልበት እርምጃ በመራጩ ላይ በተንቤንና በገሞጎፋ ተከስተዋል
በተንቤን እንደ ትላንትናዉም የሕወሃት/ኢህአዴግ ታጣቂዎች ሰማይ ላይ እየተኮሱ ህዝቡን ያሸብሩ እንደነበረም የደረሰን ዘገባ ያመልክታል። በተንቤን የአዲስ አድማስ ዘጋቢ ጋዜጠኛ ጺዎን ግርማ መታሰሯን መዘገባችን ይታወሳል። ጋዜጠኛ ጺዎን ትፈታ አትፈታ እስከ አሁን ለማረጋገጥ አልተቻለም።
በገሙጎፋ፣ ጋራ ሞላ አካባቢ የመንግስት መኪና በመጠቀም፣ መንገድ ላይ ህዝቡን በማቆም የኢሕአዴግ ታጣቂዎች የያዙትን መሳሪያ በማሳየት ኢሕአዴግ/ሕወሃትን ሰዉ ካልመረጠ ዋጋዉን እንደሚያገኝ ሲያስፈራሩ እንደነበረም ለማወቅ ችለናል።
.
ግንቦት 15 ቀን 2002 1፡30 PM ዋሺንግተን ሰዓት – 7፡30 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
የምርጫ ታዛቢዎች በብዛት እንደተባረሩ የሚገልጹ ሰፊ ዘገባዎች እየደረሱ ነዉ
ምርጫዉ ከተጠናቀቀ ሁለት ሰዓት አልፎታል። ዘግይቶ የደረሰን ዜና እንደሚያመልክተዉ በደቡብ ጎንደር ባሉ ሰባት ሰምንት የምርጫ ጣቢያዎች የነበሩ የተቃዋሚ ፓርቲ ታዛቢዎች በሙሉ ተባረዉ አንድም ታዛቢ በሌለበት ምርጫዉ ተጠናቋል።
በባህር ዳር አካባቢ ጭንብር በሚባል ቦታ ለመምረጥ የተመሰገበዉ ኢትዮጵያዊ ቁጥር 250 ብቻ ሲሆን ድምጽ የሰጠዉ ግን 300 ነዉ።
በወሎ አምባሰል አካባቢ ባሉ 76 ጣቢያዎች በአምሳ ስድስቱ ታዛቢዎች ተባረዋል። በአሰላ፣ በቢሾፍቱ፣ በጎዳጃ ጢስ አባይ አካባቢ ተመሳሳይ ሁኔታ ነበረ።
በደብረ ኤሊያ ጎጃም ሰላሳ ሁለት ታዛቢዎች ሲባረሩ አሥራ ሰባት ብቻ ነበር የነበሩት።
.
ግንቦት 15 ቀን 2002 12፡00 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 7፡00 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
የአዉሮፓ ሕብረት ታዛቢዎች በመድረክ/መኢአድ ላይ የደረሰዉ ወከባና ግፍ አላየንም እያሉ ነዉ
ዶር መራራ ጉዲና ለአሶሴየትድ ፕሬስ በሰጡት ቃለ መጠይቅ፣ በአፍሪካ ከተደረጉ ምርጫዉ ጋር ሲነጻጸርም እንኳ ይህ ምርጫ «ምርጫ» ሊባል እንደማይችል ገለጹ። ነገ፣ በዚህ በአሳዛኝ ምርጫ ላይ የመድረኩ አመራር እንደሚወያይ የጠቆሙት ዶር መራራ «አንድ ነገር ግልጽና የማያከራክር ነዉ። ይሄ ሁሉ መፈጸሙን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዉያን ያዩትና የሚመሰክሩት ነዉ» ብለዋል።
በተያያዘ ዜና የአዉሮፓ ሕብረት ታዛቢዎች ከመድረኩና ከመኢአድ እየቀረቡ ያሉ መረጃዎችን የመቀበል አዝማሚያ እንደማይታይባቸዉ የደረሰን ዘገባ ያመልክታል። ታዛቢዎቹ አዲስ አበባ ለናሙና በተዘጋጁ የምርጫ ጣቢያዎች ብቻ በመሄድ «እስከ አሁን ችግር አላየንም» በሚል ለገዢዉ ፓርቲ አለ አቀፍ እዉቅና ያሰጡታል ተብሎ ይጠበቃል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 11፡30 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 6፡30 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
ኢቲቪ ኢንጂነር ግዛቸዉን ቃለ መጠይቅ አድርጎ ወዲያዉ ቆረጠዉ
የኢትዮጵያ ቴለቭዥን የተለያዩ ተቃዋሚ ድርጅቶች ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራዉን ቃለ መተይቅ ለማድረግ ሞክረዉ ኢንጂንጀር ግዛቸዉ «ምርጫዉ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ አይደለም። ተጭበርብሯል» ብለዉ ለማብራራት ሲሞክሩ ወዲያዉ ንግግራቸዉ እንዲቋረጥ ተደረጓል።
አዲስ ነገር እንደዘገበዉ «ይህ ምርጫ እንደ ምርጫ ሊቆጠር አይችልም !» በማለት የመኢአድ ሊቀመንበር አቶ ኃይሉ ሻዉል ምርጫዉ ን ሲያወግዙት የአንድነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ስዬ አብርሃ «ደም እስካልፈሰሰ ድረስ ጦርነት አይደለም ማለት አይቻልም። እነርሱ (ኢሕአዴጎች) ደም ከማፈሰስ በቀር በጦርነት የሚደረገዉን ሁሉ አደርገዋል» ሲሉ በዛሬዉ ቀን የታየዉ ምርጫ ሳይሆን ጦርነት እንደሆነ ገልጸዋል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 11፡05 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 6፡05 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
ምርጫዉ ተብዬዉ ጨዋታ ተጠናቋል -የኤዴፓ ታዛቢዎች ሊታዩ አልቻለም
ምርጫዉን ለመታዘብ ሁለት አይነት ታዛቢዎች አሉ። የመጀመሪያ ቡድን ሕወሃት/ኢሕአዴግ በሕዝብ ተመርጠዋል ያላቸዉ አምስት ሰዎችን የያዘዉ የታዛቢዎች ቡድን ነዉ። በዚህ ቡድን ዉስጥ ያሉት በሕወሃት/ኢህአዴግ የተከፈላቸዉ የሕወሃት/ኢሕአዴግ ታዛቢዎች ተደረጎ በማንም የሚቆጠሩ ናቸዉ።
አዲስ አበባ ያሉ ዘጋቢዎቻችን እንደገለጹት በአዲስ አበባ የኢዴፓ ታዛቢዎች በጭራሽ ሊታዩ አልቻሉም። የደረሰን ዘገባ አክሎ እንደሚገልጸዉም የመኢአድና የመድረኩ ታዛቢዎች በአንድ ላይ እየሰሩ ሲሆን የመድረኩም ሆነ የመኢአድ አመራር አባላት ምርጫዉ ማወገዝ ጀምረዋል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 10፡20 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 4፡20 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
ዶር መራራ ጉዲና እንዲህ አይነት የምርጫ አፈና አይቼ አላወቅም አሉ
የመድረክ ከፍተኛ አመራር አባል የሆኑት ዶር መራራ ጉዲና የዛሬው አይነት ምርጫ እንዳዩት አይነት ወከባ ሽብር አይተዉ እንደማያወቁ ገለጹ። ዶር መራራ የመድረክ ታዛቢዎች ላይ የውጭ ወራሪ ላይ እንደሚዘመተዉ እንደተዘመተባቸዉ ገልጸዉ፣ ሕወሃት/ኢህአዴግ ድምጽሊሰርቅ እንደሚችል ቢያወቁም እንደዚህ ግን አይን ያወጣ አፈናና ማጭበርበር ያደርጋል ብለዉ ገመተዉ እንዳልነበረ አስረድተዋል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 10፡15 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 4፡45 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
በተንቤን መራጮች ካሜራ እየተቀረጹ ነዉ – የመኢአድ ታዛቢዎች በጎጃም ተደበደቡ
በተንቤን የድህንነት አባላት፣ ካድሬዎችና የታጠቁ ኃይላት ተቆጣጥረዉታል። የምርጫ ቦርድ ሃላፊዎች ሳይሆን እነዚህ ኃይላት ሰዉን ወደ መምረጫዉ ቦታ የሚያስገቡት እነርሱ እንደሆኑም የደረሰን ዘገባ ያመለክታል።
በአካባቢዉ የሚወዳደሩት አቶ ስዬ አብርሃ «በምርጫዉ ቅስቀሳ ወቅት ካሜራ እንደማይኖር ለሕዝቡ ነግረነዉ ነበር። በቆላ ተንቤን ግን የትግራይ ቲቪ የሚባለዉ ቲማ ካሜራማኖች በድምጽ መስጫ ዉስጥ ገብተዉ ይቀርጹ እንደነበረ ገልጸዋል።
የመኢአድ ማእከላዊ ኮሚቴ አባል አቶ አበባዉ መሃሪ ለአዲስ ነገር እንደዘገቡት በበርካታ የምርጫ ጣቢያዎች ታዛቢዎቻቸዉ እየተደበደቡ መባረራቸዉን ገለጹ። «ተደብድበዉ ከመባረራቸዉ በፊት ታዛቢዎቻች ኮሮጆዉ በሌላ ካርዶች ሲታጨቅ ማየታቸዉን» ገልጸዉልናል ሲሉም ገዢዉ ፓርቲ ምርጫዉ አይን ባወጣ መልኩ እያስጭበረበረ መሆኑን አጋልጠዋል።
ዶር ነጋሶ ከምርጫዉ ወጡ የተባለዉ ዉሸት ነው
የሕወሃት/ኢሕአዴግ መገናኛ ጣቢያዎች ቢቢሲ የዘገበዉ ነዉ በሚል ዶር ነጋሶ ጊዳዳ እራሳቸዉን ከምርጫዉ እንዳገለሉ መዘገባቸዉን በተመለከተ፣ ዶር ነጋሶ ጊዳዳ ዉሸት ነዉ ሲሉ ዜናዉን አጣጣሉት። በአንድነት ፓርቲ ጽ/ቤት ዉስጥ በአሁኑ ጊዜ የሚገኙት ዶር ነጋሶ፣ ቢቢሲ ደዉለዉ ወሬዉን ከነርሱ መዉጣቱን ለማረጋገጥ ሞክረዉ ቢቢሲ ከነርሱ እንዳልመጣ ፣ እንደዚያም ብለዉ እንዳልዘገቡ ገልጸዋል።
2 9፡30 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 4፡30 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
በአዳማ የመድረክና የመኢአድ ተወዳዳሪዎች እራሳቸዉን አገለሉ
በናዝሬት/አዳማ ለፓርላማ የተወዳደሩ ከመኢአድ አቶ ብርሃኑ ተሾመ ከመድረክ አቶ ጎበና ኑሩ ተወዳዳሪዎች ምርጫዉ በተደረገ በሶስት ሰዓት ዉስጥ እራሳቸዉን ከምርጫዉ እንዳገለሉ የደረሰን ዘገባ ያመለክታል። ታዛቢዎቻቸዉ እንዳይሳተፉ በመደረጉና የኢሕአዴግ ካድሬዎች ከፍተኛ ግፍና ወከባ እየትይፈጸሙ በመሆኑ ምርጫዉ ምርጫ ሳይሆን ጦርነት እንደሆነ በመናገር ነዉ ከምርጫዉ የወጡት።
ግንቦት 15 ቀን 2002 9፡00 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 4፡00 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
ኢንጅነር ኃይሉ ሻዉል ምርጫዉ ተሰርቋል አሉ
የመኢአድ ሊቀመንበር ኢንጂነር ኃይሉ ሻዉል በአባላቶቻቸዉና በታዛቢዎቻቸዉ ላይ ከፍተኛ ጫናና ወከባ እንደደረሰባቸዉ በመግለጽ ምርጫዉ ፍትሃዊና ዴእሞክራሲያዊ እንዳልሆነ እንደተሰረቀ እየተናገሩ እንደሆነ የደረሰን ዘገባ ያመለክታል።
ኢንጂነር ግዛቸዉም በበኩላቸዉ ምርጫዉ ፍትሃዊና ዴሞርካሲያ አይደለም ሲሉ አዉግዘዉታል።
የአንድነት ፓርቲ ተጠባባቂ ሊቀመንበር ኢንጂነር ግዛቸዉም ምርጫዉ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ እንዳልሆነ ይፋ አደርገዋል። በዚህም የተነሳ የምርጫ ቦርዱ ሃላፊ በድንገት ድምጽ መስጠት ሳያልቅ እንዴት ምርጫዉ ተሰርቋል ይበላል በሚል የወገዛ መግለጫም ሰጥተዋል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 – 6፡00 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 1፡00 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
ዶር ነጋሶ «ምርጫዉን ላንቀበለዉ እንችላለን» አሉ – ጋዜጠኛ ጺዎን ግርማ በተንቤን ታሰረች
ዶር ነጋሶ ጊዳዳ ላለፉት ሲስት ሰዓታት የነበረዉን የምርጫ ሂደት በመታዘብ ምርጫዉን ላንቀበል እንችላለን ሲሉ ሁኔታዉ እጅግ በጣም አሳሳቢ እንደሆነ ገለጹ። በሌላ ዜና ምርጫዉን ለመዘገበ በተንቤን የምትገኘዉ የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዘጋቢ ጋዜጠኛ ጽዩን ግርማ በተንቤን ታሰራለች።
በሰበታ የኦሮሞ ክልል ከፍተኛ ጥበቃ እየተደረገ ነዉ። የመድረክ አራባ የሚሆኑ ደጋፊዎች ማዞሪያ በሚባል ቦታ ታፍሰዉ ትይዘዋል።
በተለያዩ የአገሪቱ ግዛቶች መድረኩ ያሰማራቸዉ ታዛቢዎች «ከምርጫና ከሕይወትህ ምረጥ» በመባላቸዉ 20፣ 15 ኪሎሜትር ርቀዉ ከሚታዘቡበት ቦታ እየለቀቁ ወደ ከተማ እየገቡ መሆኑን ለማረጋገጥ ችለናል።
በፍቼ የመድረኩ ተወዳዳሪ ወ/ሮ አስናቀች «በጣም ሁከትና ጭንቀት የተሞላበት» ሲሉ ምርጫዉ ምን ያህል አስቸጋሪ እንደሆነ ገልጸዋል። ታዛቢዎቻቸዉ እንዳይታዘቡ በተደረገበት ሁኔታ የሚደረገ ምርጫ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ አይደለም ብለዉታል። በመሆኑ ወ/ሮ አስናቀች «ከዚህ የሚገኘዉ ዉጤትና ምርጫዉን ልንቀበል አንችልም» ሲሉ ድርጊቱን አሳፋሪ ብለዉታል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 – 5፡30 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 12፡30 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
በጎጃም ታዛቢዎች የት እንደገቡ አይታወቅም- ምርጫዉ ምርጫ ምርጫ አይሸትም ተባለ
በምእራብ ጎጃም የደረሰን ዘገባ እንደሚያመልክተዉ በዚያም መድረኩ ያሰማራችዉ ታዛቢዎች ከፍተኛ ወከባና እንግለ\ልት እየደረሰባቸዉ ነዉ። በሰሜን ኢትዮጵያ የአንድነት ፓርቲ አደራጅና የፓርላማ አባል አቶ ኃይለየሱስ ከአራባ በላይ የምርጫ ጣቢያዎች እንደተከታተሉ ገልጸዉ ምርጫዉ «እጅግ በጣም ከባድ አስቸጋሪ ሁኔታ ላይ ነዉ ያለዉ» ሲሉ መድረኩ ያዘጋጃቸዉ ታዛቢዎች ከአቅማቸዉ በላይ በሆኑ ጫናዎች እንዲለቁ እየተደረገ እንደሆነ ገልጸዋል።
ታዛቢዎችን ሃሙስ እንዳሳወቁ የገለጹት አቶ ኃይለየሱስ ምርጫ ቦርድ የታዛቢዎቻችንን ስም ዝርዝር ለሕወሃት ካድሬዎች በመስጠቱ ሌሊት ሁሉ ሳይቀር በየቤታቸዉ እየሄዱ በቤተሰቦቻቸው ላይ ሁሉ ዛቻ እንደቀረበ ገልጸዋል።
በጎጃም በጂዳ ወረዳ አንድ ታዛቢ በደብረ ማርቆስ ሁለት ታዛቢዎች የት እንደገቡ አይታወቅም።
በጎንደር በደባቅ፣ በክምር ድንጋይ መድረኩ ያዘጋጃቸዉ ታዛቢዎች በሙሉ አልተገኙም። በጠቅላላ ምርጫዉ «ምርጫ፣ ምርጫ» እንደማይሸት እየተነገረ ነዉ። በምርጫ ጣቢያዎች ሁሉ የመድረኩ ታዛቢዎች በጉቦ፣ በማስፈራራት እንዳይገኙ እየተደረገ ነዉ። የተገኙትም በመታሰር ላይ ይገኛሉ።
በኢትዮጵያ እየተደረገ ያለዉ ምርጫ ምርጫ ሳይሆነ ጦርነት እንደሆነ በግልጽ እየታየ ነዉ።
በተያያዘ ዜና በወልቃይት ጠገዴ የመድረኩ ተወዳዳሪ የሆኑት አቶ ዘነበ ሲሳይ ከቤታቸዉ እንዳይወጡ ታግተዉ እንደነበረ መዘገባችን ይታወሳል። አቶ ዘነበ ከቤታቸዉ መዉጣትና መንቀሳቀስ እንደቻሉና እንደመረጡም ለማረጋገጥ ችለናል። እንደዚያም ቢሆን ግን አሁንም መለዮ የለበሱ ታጣቂዎች በቤታቸዉ ዙሪያ እንደሚገኙ ከስፍራዉ የደረሰን ዜና ያመለክታል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 – 5፡00 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 12፡00 PM ኢትዮጵያ ሰዓት
ሕወሃት ታዛቢዎቻችን በማስፈራራቱና በማስጨነቁ ሁሉ ሊገኙ አልቻሉም – ወ/ሮ አረጋሽ
የህወሃት/ኢሕአዴግ መሪ አቶ መለስ ዜናዊ በሚወዳደሩበት የአድዋ ወረዳ መድረኩ ያዘጋጃቸዉ ታዛቢዎች በሙሉ ከገዢዉ ፓርቲ በደረሰባቸዉ ጫናና እንግልት ምክንያት እንዳልተገኙ ታወቀ። የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ የታዛቢዎች ስም ዝርዝር ለህወሃት/ኢሕአዴግ አስቀድሞ በመስጠቱ የሕወሃት ካድሬዎች በየታዛቢዎች ቤት እየሄዱ በቤተሰቦቻቸው ላይ ሁሉ ሳይቀር ጉዳት እንደሚመጣ ሲያስጠነቅቁና ሲዝቱ እንደነበረ መዘገቡ ይታወቃል።
በዚህ ጉዳይ ላይ አስተያየት የሰጡት የመድረኩ ተወዳዳሪ ወ/ሮ አረጋች ይህ ምርጫ፣ ገዢዉ ፓርቲ የሚለዉ ሌላ፣ ተግባሩ ግን ሌላ መሆኑን ያጋለጠ ምርጫ ነዉ ብለዉታል። መድረኩ በከተማዉ የለጠፋቸዉ የመድረክ አርማ ያለበት ፓስተሮች በሙሉ እንደተነቃቀሉ የገለጹት ወ/ሮ አረጋሽ በየቦታዉ የሚታየዉ የሕወሃት/ኢሕአዴግ የንብ አርማ ብቻ ነዉ ብለዋል። «በአድዋ ምርጫ የሚደረግ አይመስልም» ያሉት ወ/ሮ አረጋሽ በመራጩ ሕዝብ ላይ ሁሉ ሳይቀር የሕወሃት ካድሬዎች ቡድን በቡድን በመሆኑ «ከንቧ ዉጭ ሌላ ሰዉ ትመርጡና ግንቦት 16 ቀን እንገናኛለን» እያሉ እንደሚያስፈራሩ ገልጸዋል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 – 4:00 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 11:00 AM ኢትዮጵያ ሰዓት
በወላይታ ሶዶ ምርጫዉ እንደተጭበረበረ ተገለጸ – ከአርባ የሚበልጡ ታዛቢዎች ታስረዋል
በአዲስ አበባ የምርጫዉ ሂደት የከፋ ብዙ ችግር ባይታይበትም በቦሌ፣ በቃሊቲ፣ በፈረንሳይ ለጋሲዮን፣ በኮተቤና በሌሎች በአንዳንድ ወረዳዎች የገዢዉ ፓርቲ ካድሬዎች በቡድን በቡድን በመሆን ህዝቡን እንደሚያስፈራሩና በሕዝቡ ላይ እንደሚዝቱ የደረሰን ዘገባ ያመለክታል።
የነዚህ ካድሬዎች ተግባር በጣም አስቸጋሪ ከመሆኑ የተነሳ በአንዳንድ ወረዳዎች የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ እንዲያውቀዉ ተደረጎ ምርጫ ቦርድ የጸጥታ ኃይሎች በመላክ ለማረጋጋት እንደቻለም ለማወቅ ችለናል።
የአዲስ አበባዉ በዚህ ሁኔታ ላይ እንዳለ በክፍለ ሃገር አፈናዉና አይን ያወጣዉ ዘረፋ በገሃድ እየታየ ነዉ። በደቡብ ወሎ ምርጫ ከመጀመሩ በፊት ኮሮጆዎች ሞልተዉ የመድረኩ ታዛቢዎች «አታስፈልጉም» ተብለዉ የምርጫ ቦርድ የሰጣቸዉን ካርዳቸዉን ተነጥቀዉ ተመልሰዋል። በደቡብ ጎንደር ሶስት የመድረኩ ታዛቢዎች ታስረዋል። በፍቼ አንድ የመድረኩ ታዛቢ ታስረዋል።
በወላይታ ሶዶ የመድረኩ ተወዳዳሪ ወ/ሮ ጸሃይ ምርጫዉን «ፍጹም የተጭበረበረ» ብለዉታል። በወላይታ ሶዶ ትላንት ለመድረኩ ታዛቢዎች አበል ከፍለዉ ዛሬ ይታዘባሉ ተብሎ ሲጠበቅ እንደታሰሩ አረጋግጠናል።
እስከ አሁን በወልቃይት ጠገዴ አንድ የመድረኩ ተወዳዳሪ ሲታሰር 32 ታዛቢዎች በወላይታ ሶዶም በርካታ ታስረዋል። (28 በባሌ፣ ሶስት በደቡብ ጎንደር አንድ በፍቼና ቁጥራቸዉ ገና ያልታወቀ በወላይታ ሶዶ)
በሰሜን ወሎ የክልሉ አስተዳዳሪዎች መራጮች እጃቸዉን ይዘዉ «እዚህ ላይ ምረጡ» እስከመባል የደረሱ ሲሆን «የምርጫ ወረቀቶች ለሰዎች አስቀድመዉ ተሰጥተዉ፣ ሰዎች ሞልተዋቸዉ ሲመጡ አግኝተናቸዋል» ሲሉም በአካባቢዉ ያሉ የመድረክ ታዛቢዎች ይናገራሉ።
ግንቦት 15 ቀን 2002 – 3:30 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 10:30 AM ኢትዮጵያ ሰዓት
በፈረንሳይ ለጋሲዮን ባሉ ጣቢያዎች ህዝቡ እንደ ዘጠና ሰባት አልወጣም !
ከአዲስ አበባ የሚደርሱ ዘገባዎች እንደሚገልጹት ከእናቶችና ከትላልቅ ሰዎች በስተቀር ብዙ ወጣቶች እንዳልመጡ ይጠቁማሉ። በአንድ ወረዳ ወደ 52 የሚሆኑ ጣቢያዎች አሉ። አንዳንድ ጣቢያዎች አነስ ያሉ ሰልፎች ቢታዩም ከሞላ ጎደል እስከ አሁን በታየዉና ከምርጫ ዘጠና ሰባት ጋር ሲነጻጸር ህዝብ የተሳተፈበት አይደለም።
የወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ሰፈር ያሉ ሁለት የምርጫ ጣቢያዎችን ከዉጭ አገር ጋዜጠኞች ጋር የታዘበዉ ጋዜጣኛ እስክንድር ነጋ በታዘባቸዉ ጣቢያዎች ይሄ ነዉ የሚላቸዉ ችግር እንዳላየ ገለጸ።
እንደዚያም ሆኖ ግን ከምርጫ ዘጠና ሰባት እንደነበረዉ ሰዉ ለመምረጥ በስፋት እንዳልመጣ ገልጿል። «በምርጫ ዘጠና ሰባት ሰልፍ ነበር። አሁን ሰልፍ የለም» የለም ያለዉ አቶ እስክንድር በተለይም የወጣቱ ተሳትፎ ቀዝቃዛ እንደሆነ ነዉ ያስረዳዉ።
ለመምረጥ የመጡት ጥቂቶች ማንን እንደመረጡ ቢጠየቁ ማንን እንደመረጡ ለመንገር ፈቃደኛ እንዳልሆኑ የገለጹት አቶ እስክንድር የአገዛዙ ካድሬዎች ሰዉን ስናዋራ በሞባይል ቪዲዎ ስለሚቀርጹ ሰዉ ፈርቶ «የመረጥነዉን መርጠናል» የሚል ምላሽ እንደሚሰጥ ገልጸዋል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 – 2:30 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 9:30 AM ኢትዮጵያ ሰዓት
በወሎና በጎንደር የመድረኩ ታዛቢዎችን በመደብደብ እንዳይታዘቡ እየተደረገ መሆኑን የደረሰን ዘገባ ያመልክታል።
በአዲስ አበባ በምርጫዉ ደንብ መሰረት ከጠዋቱ 11 ሰዓት እሰክ 12፡00 ሰዓት ኮረጆዎች ባዶ መሆናቸዉንና ለምርጫ የሚመች ሁኔታ መኖሩን ታዛቢዎች የሚመለክቱበት ጊዜ ነበር። ነገር ግን ያነጋገርናቸዉ አቶ አንዱዋለም አርጌ እንደገለጹት የመድረኩ ታዛቢዎች ከ11፡00 ሰዓት በፊት ሲደርሱ ሁሉ ነገር ተጠናቆ ምርጫዉ መጀመሩን ገልጸዋል። ኮሮጆዎች ባዶ መሆናቸዉን የመድረኩ ታዛቢዎች በብዛት አለማረጋገጣቸዉን፣ የገለጹት አቶ አንዱዋለም በበርካታ የምርጫ ጣቢያዎች ኮሮጆዎች ሆን ተብሎ በመስኮት አካባቢ እንደተደረጉም ገልጸዋል።
የምርጫዉ ድንኳኖችን በተመለከተ አንድ ድንኳን ለሁለት የተከፈለ ሲሆን የድንኳኑን አንድ ክፍል ከሌላዉ በሚለየዉ ቦታ ላይ የምርጫ ሰራተኞች እንደሚቆሙም የነገሩን አቶ አንዱዋለም፣ ይህ ሕዝቡ እንዲፈራ ሆን ተብሎ የተደረገ እንደሆነ ገልጸዋል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 – 2:00 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 9:00 AM ኢትዮጵያ ሰዓት
በደቡብ ምርጫዉ ከቁጥጥር ዉጭ ሆኗል – የተሞሉ ኮረጆዎች እየታዩ ነዉ – ዶር በየነ
በደቡብ ክልል ዶር በየነ ምርጫዉ ከቁጥጥር ዉጭ ሆኗል አሉ። በወላይታ በሃዲያ በከንባታ በምእራብ አርሲ እንዲሁም በበርካታ የደቡብ አካባቢዎች ሕዝቡ ከመምረጡ በፊት ተቀደዉ የተሰፉ፣ በአንዳንድ ቦታዎችም የተሞሉ ኮረጆች እንዳሉ ዶር በየነ ገልጸዋል። የመድረኩ ታዛቢዎች ለመታዘብ ሲሄዱ እየተደበደቡ እንደተመለሱም ያስረዱት ዶር በየነ የአዉሮፓ ሕብረት የደቡብ ተወካዮችን ለማግኘት ሞከረዉ እንዳልተሳካላቸዉ ገልጸዋል።፡
«የአዉሮፓ ሕብረት አንድም ቦታ አልታዩም። የአዉሮፓን ሕብረት የሚያስተባብሩት ስልክ አያነሱም» ያሉት ዶር በየነ ድርጊቱን አሳዛኝና አሳፋሪ ነዉ ብለዉታል። ምርጫዉ ትልቅ ችግር እንዳለበትና ከቁጥጥር ዉጭ እንደሆነ ዶር በየነ አስረድተዋል።
በሃገረ ማሪያም ሲዳሞ የመድረኩ አደራጅ አቶ ጌታቸዉ በቀለ አፈናዉ ከፍተኛ መሆኑን ሲገልጹ በአራት የምርጫ ጣቢያዎች የመድረኩ ታዛቢዎች እንደተባረሩ ገልጸዉ አንድ ታዛቢ እንደታሰሩም አስረድተዋል።
ዛሬ የምርጫ ቀን ቢባልም ጦርነት ነዉ እየተካሄደ ያለዉ – የጦርነት ቀን ነዉ
ግንቦት 15 ቀን 2002 – 1፡ 45 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 8:45 AM ኢትዮጵያ ሰዓት
23 ታዛቢዎች በበባሌ ጎባ ታሰሩ – በተንቤን ትላንት ታጣቂዎች ተኩስ ከፈቱ
ምርጫዉ በአገሪቷ በሙሉ ተጀምሯል። በርካታ ችግሮች እየታዩ ነዉ። በባሌ ጎባ 23 የመድረኩ ታዛቢዎች በሕወሃት/ኢሕአዴግ የደህንነት አባላት ታስረዋል። በወልቃይት ጠገዴ የመድረኩ ተወዳዳሪ በሁለት ታጣቂዎች ታግተዋል። ቤታቸዉ ስልክ ለመደወል የተሞከረዉ ሙከራ ሊሳካ አልቻለም። «ከአገልግሎት ዉጭ» የሚል ምላሽ ነዉ የተገኘዉ።
በፍቼ መድረኩን ወክለዉ የሚወዳደሩትና በቅርብ ታስረዉ የተፈቱት የወ/ሮ አስናቀች መኪና ፍሬን ተበጥሶ አድሯል። ወ/ሮ አስናቀች በጋሪ ታዛቢዎቻቸዉን ለማድረስ ትልቅ ሙከራ እንዳደረጉም የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
ትላንት ግንቦት 14 ቀን በተንቤን ወርቃባ ብዙ ሕዝብ ንግድ በሚያደርጉበት ቦታ በተፈጠረዉ ቀዉስ የደህንነት አባላት ወደ ሰማይ ተኩስ ይተኩሱ እንደነበረም መረጃ ደርሶናል። በዚህም ምክንያት በርካታ የአቶ ስዬ አብርሃ ታዛቢዎች ሊበታተኑ ችለዋል። «ያሉትን በሙሉ እንደምንም ብለን አሰባስበን በሌላ መኪና ስናሰማራችዉ መኪናዉን መንገድ ላይ አስቁመዉ አገቱት» ያሉት አቶ ስዬ ጉዳዩን ለአዉሮፓ ሕብረት እንዳሳወቁ ገልጸዋል።
ከጥቂት ሰዓታት በፊት አቶ ስዬ በሚመርጡበት ቀበሌ ኮረጆዎች ተራርቀዉ ከመቀመጣቸዉ ሰዉ ሊመርጥ ሲዘጋጅ 3፣ 4 ሆኖ በቡድን በመቆም ሕዝቡን የማስፈራራት ነገር እንደነበረ ገልጸዋል።
ግንቦት 15 ቀን 2002 – 12፡ 00 AM ዋሺንግተን ሰዓት – 7:00 AM ኢትዮጵያ ሰዓት
በአጠቃላይ ከአርባ ሁለት ሺህ በላይ የምርጫ ጣቢያዎች ያሉ ሲሆን ለዚያ ሁሉ ጣቢያ የተመደቡት ገለልተኛ የዉጭ አገር ዘጋቢዎች መቶ አምሳ ብቻ ናቸዉ። ባለፈዉ የዘጣና ሰባት ምርጫ ከ250 በላይ የአዉሮፓ ሕብረት ከመቶ አምሳ በላይ የካርተር ሴንተር ታዛቢዎች ነበሩ።
በተጨማሪ ገለልተኛ የሆኑ አገር በቀል የሲቪክ ማህበራትም ምርጫዉን ለመታዘብ ተሰማርተዉ ነበር። የአሁኑ የ2002 ምርጫ ግን፣ ካለፈዉ ምርጫ በብዙ መልኩ የተለየ ነዉ። ገዢዉ ፓርቲ ምርጫዉን ለመስረቅና ለማጭበርበር እንዲያመቸዉ የሚያደርጉ ዝግጅቶች የተጠናቀቁ ይመስላል። በዚህም ምክንያት ምርጫዉ ሕወሃት/ኢሕአዴግ የሕዝብን ልብ አግኝቶ በማሸነፍ ሳይሆን በማጭበርበር አሸነፍኩ እንደሚል የሚገምቱ ብዙ ናቸዉ።
እንደዚያም ሆኖ ተአምር መስራት የሚችለዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ የዛሬዉን ምርጫ ተጠቅሞ ሊነቃነቅ እንደሚችልም የሚናገሩ አሉ። ዉጤቱን እንግዲህ በቅርብ የምንከታተለዉ ይሆናል።
ግንቦት 14 ቀን 2002 – 11፡o0 PM ዋሺንግተን ሰዓት – 6:00 AM ኢትዮጵያ ሰዓት
የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ ታፈነ
ወያኔ ኢሕአዴግ ሙሉ ለሙሉ የሚቆጣጠረዉ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ምርጫዉን በተመለከተ ከጠዋቱ ጀምሮ እስከ እኩለ ሌሊት ለመዘገብ በአገሪቷ ዘጋቢዎችን በስምንት ቡድን ከፍሎ ማሰማራቱን ለተመልካቾቹ ገለጸ።
በተቃራኒዉ የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ እንደ አሜሪካን ድምጽ ሬድዲዮ ሁሉ በመታፈኑ ካለፈዉ አርብ ጀምሮ እንደማይሰማ ከአዲስ አበባ የደረሰን ዘገባ ያመለክታል። ይህም የወያኔ/ኢሕአዴግ ካድሬዎች የሚፈልጉት ኢንፎርሜሽን ብቻ ለሕዝቡ እንዲደርስ ለማድረግ ሆን ብለዉ ያደረጉት መሆኑ ጥርጥር የለዉም።
ግንቦት 14 ቀን 2002 – 3፡30 PM ዋሺንግተን ሰዓት
የሕወሃት/ኢሕአዴግ ታጣቂዎች የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ተጠባባቂ ሊቀመንበር ኢንጂነር ግዛቸዉ ሽፈራዉ፣ የአንድነት ፓርቲ ዋና ጸሃፊዉ አቶ አንዱዋለም አርጌ እንዲሁም በርካታ የመድረክ አመራር አባላት በሕወሃት/ኢሕአዴግ ታጣቂዎች የጠበቀ ክትትል ዉስጥ እንዳሉ ከስፍራዉ የደረሰን ዜና ያመለክታል።
የመድረክ አመራር አባላትን በመኪና ከኋላ በመከታተልና በቤታቸዉ ዙሪያ በማንዣበብ ከሚያደርጉት የማስፈራራት ዘመቻ በተጨማሪ የሕወሃት/ኢሕአዴግ ካድሬዎች መድረክን ወክለዉ ምርጫዉ ለመታዘብ ፍቃደኛ የሆኑ ሰላማዊ ኢትዮጵያዉያን ዜጎች ላይ ከፍተኛ የሆነ ዛቻና ማስፈራራት እያደረሱ እንደሆነ የደረሰን ዘገባ አክሎ ይገልጻል። በተለይም አፈናዉ\ በኦሮሚያ በስፋት እየተያ ሲሆን በጎንደር፣ በወሎና በምስራቅ ጎጃም የሕወሃት/ኢሕአዴግ ካድሬዎችና ባለሥልጣናት፣ መድረኩን ወክለዉ የሚታዘቡ ወገኖችን «ሰኞ ከቤታችሁ ሬሳ ይወጣል» እያሉ እየዛቱባቸዉ እንደሆነም ለማረጋገጥ ለማወቅ ችለናል።


Leave a Reply